ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያህ - ረሒመሁላህ - ሲሞቱ ጊዜ ታስረውበት በነበረው ወህኒ ቤት ውስጥ በሳቸው የእጅ ፅሑፍ የተፃፉ እንዲህ የሚሉ አሳዛኝ የግጥም ስንኞች ተገኝተዋል። በግርድፉ ተርጉሜዋለሁ።

“እኔ ነኝ ደካማው ከጃይ … ከሰማያቱ ባለቤት

በሁለመናዬ ስንኩል … እኔው ነኝ ምስኪኑ ማለት።

እኔው ነኝ የራሴ ጠላት … ነፍሴ እራሷ ነች በዳዬ

ኸይር ሁሉ የሚገኘው … ከሱ ብቻ ነው ጌታዬ።

ለራሴ እንኳን የማልሆን … የማላቀርብ አንዳች ፋይዳ

መከላከል አይሆንልኝ … በክፉ እንዳልጎዳ።

ሌላ ፈጣሪም የለኝ … ከሱ ውጭ ‘ሚያስተናብር

አማላጅም አይኖረኝ … ወደ ጌታ የሚያሻግር

በሱ ፈቃድ ቢሆን እንጂ … በፈጠረኝ በረሕማኑ

የሰማያቱ ባለቤት … እንዳወሳው በቁርኣኑ

ቅንጣት የሌለኝ ከንቱ … ያለ ጌታዬ ይሁንታ

አንዳች ተጋሪም የለው … በየትኛውም ሁኔታ

አጋዥ አይፈልግ ደጋፊ … ረዳት አይሻ የኔ ጌታ

ልክ እንደሚያስፈልጋቸው … ለወልዮቹ አይነታ።

ችግር ድህነት አርማዬ … የኔ ቋሚ መገለጫ

መብቃቃቱ የጌታ ነው … የሁልጊዜ ባለብልጫ

አንጋጣጭ ነው ወደ ጌታ … ፍጡር ሲባል ጠቅላላ

ሁሉም ተዋርዶ ይቀርባል … ቢሻው ጠላ ቢሻው ደላ።

ከፈጠረው ጌታ ውጭ … ምኞት ፍላጎት የሚሻ

ቂል፣ በዳይ፣ አረመኔ … አጋሪ ነው መጨረሻ።

ይመስገነው ፈጣሪዬ … አለሙን በፀጋው የሞላ

ላለፈውም ለመጪውም … ላደረገልን በመላ።

ከዚያም ሶላቱ ይትረፍረፍ … በምርጡ ነቢያችን ላይ

የፍጡራን ቁንጮ አይነታ … የሁሉ ላይ የላይ በላይ።” [አልዑቁድ፡ 391]

=

* ቴሌግራም ቻናል፡- https://t.me/IbnuMunewor

* ፌስቡክ፦ https://www.facebook.com/Ibnu.....Munewor?mibextid=ZbW

* ዋትሳፕ፦ https://whatsapp.com/channel/0....029VaA3X1e5kg7BlsJbo

* ኡማ ላይፍ፦ https://ummalife.com/IbnuMunewor

image
Send as a message
Share on my page
Share in the group