Translation is not possible.

Follow & Share → Umma ሚዲያ

↓↓↓↓↓

Umma ሚዲያ

ሁለቱም ማዶ ለማዶ ተፋጠዋል፤ የግመሎቹ ባለቤት ለሚወስደው

ማንኛውም እርምጃ ሰውዬአችን አፀፋውን ለመመለስ ቀስቶቹን

ወጥሯል።

ከርቀት የቆመው መልከ-መልካም ወጣት፦«እስቲ ከጎንህ ያለውን

ልጓም አንጠልጥልልኝ» አለው።

ሰውዬው ልጓሙን አንስቶ ሲያንጠለጥለው ሶስት ቋጠሮዎች

ከገመዱ ላይ ይታያሉ።

ወጣቱም በራስ መተማመን እፊቱ ላይ እየተስተዋለ፦«በየትኛው

ቋጠሮ ላይ ቀስቴን እንድሰካ ትፈልጋለህ...?»

ሰውዬው ግራ በመጋባት ገመዱ ላይ ተቋጥረው ከሚታዩት

የመሀከለኛዋን አመላከተው። ወጣቱም ከርቀት የቀስቱን

ማስወንጨፍያ ስቦ ፍላፃዋን ከመሀልኛው ቋጠሮ ላይ ሰካት።

እንዲህ እንዲህ እያለ በሶስቱም ቋጠሮዎች ያለምንም መሳት

ቀስቶቹን ከርቀት ሰክቶ በፍልምያም ሆነ በውግያ አቅሙን

አሳየው።

ሰውዬአችን ማመን የማይችለውን በአይኑ ሲመለከት የታጠቀውን

ሰይፍ እና ቀስቶች ወደ መሬት ጥሎ ፈዞ ማየት ጀመረ።

ወጣቱም ወደ ሰውዬው በመምጣት ሰይፉን እና ቀስቱን

ተቀብሎት ፈረስ ላይ ጭኖ ይዞት ሄደ።

«አሁን በቁጥጥሬ ስር ውለሀል። ምን ማደርግህ ይመስልሀል?»

ወጣቱ ጠየቀው።

«ትበቀለኛለሃ!» አለው ሰውዬአችን።

«ለምን?» ወጣቱ ጠየቀ።

«ያው ለሰራሁት ዝርፍያ እና በደል ነዋ፤ አሁን ፈጣሪ

አመቻችቶልሀል ትበቀለኛለህ» አለው።

ወጣቱም፦«እንደው ከሙሀልሂል ዘንድ ማዕድ ተጋርተህ፣ አብረህ

አድረህ የምበቀልህ ይመስልሀል?»

ሰውዬው በዝና የሚያውቀውን ስም ሲሰማ ድንግጥ አለ፦«አንተ

ዘይዱል ከይል ነህ?»

«አዎን» ወጣቱ መለሰለት።

«እባክህ መጥፎ አጋች አትሁነኝ» ሰውየው ይማፀን ጀመር።

«ስጋት አይግባህ!» አለ ወጣቱ።

ረጅሙን ጉዞ ከተጓዙ በኋላ ሽማግሌው ከሚገኙበት ስፍራ

ደረሱ።ከኋላቸው በርካታ ግመሎችን አስከትለዋል።

ወጣቱ ወደ ሰውዬአችን ዞር አለ ና፦«እምልልሀለሁ፤ እነዚህ

ግመሎች የኔ ቢሆኑ ሁሉንም እሰጥህ ነበር። ግና የእህቴ ነው።

ባይሆን ጥቂት ቀናት እኔ ዘንድ ትቆያለህ፤ እንዲያው ሰሞኑን አንድ

የምዘምተው ወረራ አለኝና ያን ምርኮ በሙሉ ላንተ እሰጥሀለሁ።»

ተስማሙ። በእንግድነት ልክ 3 ቀናትን እንዳሳለፈም ወጣቱ

ትጥቁን ታጥቆ አንድ ሙሉ መንደር ላይ በመዝመት ከ 100 በላይ

ግመሎችን ማርኮ እየነዳ መጣ።

ያመጣቸውን የምርኮ ግመሎችም አንዳች ሳይቀንስ ለሰውዬአችን

አስረክቦ ሰውዬውንም እስከ ቀዬው ድረስ የሚያደርሱትን

አገልጋዮች ጨምሮ ሸኘው።

ወራትን የሚወልዱት ቀናት እየተፈራረቁ በርካታ አመታትን ወልደው

አስቆጠሩ፤ አመታት እየነጎዱ በአመታት ተተኩ።

ወጣቱ ዘይድ የወጣትነትን እድሜ ተሻግሮ ግርማ ሞገስ ያለው

ጎልማሳ ሁኗል። ከእለታት አንድ ቀን ሙሀመድ ስለተባለ ነብይ

ይሰማው የነበረውን መረጃ በአካል ሄዶ ለማረጋገጥ የቀዬውን

መሳፍንት አማከራቸው። አብረው መዲና ለመሄድም ተስማሙ።

ዘይዱል ከይር ከቀዬው መሳፍንቶች ጋ ሁኖ ልክ መዲና እንደገባ

የጉዞ አዋራውን ከጀርባው ሳያራግፍ ወደ ነቢ ሰዐወ መስጅድ

አቀና።

ከመስጅዱ ቅጥር ግቢ እንደገቡም ፈረሶቻቸውን ከደጃፍ አስረው

ወደ መስጅዱ ዘልቀው ሲገቡ ቀና ብሎ ለማየት የሚያጓጓው

ነብይ ከሚንበር ላይ ቁመው ኩጥባ እያደረጉ ተመለከቱ።

ነቢ ሰዐወ ኩጥባቸውን ቀጥለዋል፦«ህዝቦቼ ሆይ! እኔ

ከአማልክቱ ዑዛ እሻላችኋለሁ። እኔ ከምታመልኳቸው ጥቋቁር

ግመሎች ለናንተ የተሻልኩ ነኝ»

ውዴ ንግግራቸውን ቀጥለዋል። ዘይድ በትኩረት አይኑንም

ጆሮውንም ሰጥቶ እያዳመጠ ነው፤ ግና የኢማን ስፍር መለክያዋ

ለከፊሉ ኢማንን ወፍቃ ለተቀሩት ክህደት ላይ ክህደትን

በመጨመር ዘይድንም ከኢማን ሰዎች መደበችው።

ከመሀከላቸው አንደኛው መሳፍንት ወደ ጓደኞቹ ጠጋ ብሎ፦«እኔ

ይህ ሰው መላ ዐረብን እንደሚቆጣጠር ምንም ጥርጥር የለኝም፤

እኔ ደሞ በአረቢያ ምድር ተቀምጬ በዚህ ።ሰው ቁጥጥር ስር

መዋልን ስለማልፈልግ ፀጉሬን ተልጬ ከደማስቆ ገዳም

እከትማለሁ » ብሎ ከተወሰኑ ጓደኞቹ ጋ ትቶ ሄደ።

ዘይድ እና የተወሰኑ ጓደኞቹ እዝያ ኩጥባው እስኪጠናቀቅ ረግተው

ተቀመጡ። ልክ ነቢ ሰዐወ ከሚንበራቸው ሲወርዱ ዘይድ ብድግ

ብሎ ድምፁን ከፍ በማድረግ፦« ሙሀመድ ሆይ! በአላህ ጌትነት

ያመንኩ ስሆን ባንተ መልዕክተኝነትም አምኛለሁ» አለ።

ነቢ ሰዐወ ሰልፉን እያቆራረጡ ወደ ዘይድ መጡ ና፦«ማን ነህ?»

አሉት።

«እኔ ዘይዱል-ከይል የሙሀልሂል ልጅ ነኝ»

«አይ አንተ ዘይዱል ከይል ሳትሆን ዘይዱል ከይር ነህ። ጋራ

ሸንተረሩን አቆራርጦ ሊኢስላም ቀልብህን ከፍቶ ያመጣህ አላህ

ምስጋና ይገባው» አሉ።

ነቢ ሰዐወ እንግዳ አክባሪ ናቸው። እንግዳቸውን እና የተወሰኑ

ሰሀባዎችን ይዘው ወደ ቤታቸው ሄዱ። ዘይድ ልክ ነቢ ሰዐወ ቤት

ገብቶ ከመደቡ ላይ አረፍ ሲል ነቢ ሰዐወ ትራስ አቀበሉት።

ከሳቸው ፊት ሁኖ ትራስ ላይ መንተራስ የከበደው ዘይድም ትራሱን

መልሶ ሰጣቸው፣ መልሰው ሰጡት፣ መልሶ ሰጣቸው፣ መልሰው

ሰጡት።

ከዝያ ተረጋግተው ማውጋር ጀመሩ።

«ዘይድ! እኔ ብዙ ሰው ባህሪው ከሩቅ ተነግሮኝ በአካልም

ተመልክቼዋለሁ። ግን ዝናውን ሰምቼ በአካልም ሳገኘው ከዝናው

ጋር እንዳንተ የተመሳሰለብኝ ሰው የለም። እና እንዴት ነህ?...»

ነቢ ጫወታ ያውቃሉ እኮ።

«ያው መልካምን እና ሰሪዎቹን እወዳለሁ። መልካም ነገር ሰርቼ

ስጨርስ እረካለሁ፤ ሲያመልጠኝም እቆጫለሁ» አላቸው።

«ይኼማ! አላህ በመረጣቸው ባሮች ላይ የሚያደርገው መለያ

ምልክት ነው» አሉት።

ወደሳቸው ዞር ብሎ፦«አላህ እና መልዕክተኛው በሚሹት ነገር ላይ

ላዋለኝ አላህ ምስጋና ይገባው።

ባይሆን እስቲ 3 መቶ ፈረሰኞችን ይስጡኝና የሮም ስረወ

መንግስትን ደምስሼ ምርኮውን ላምጣ።» አላቸው።

ነቢ ሰዐወ ነገሩ ገነነባቸው ና፦« አይ!!! ዘይድ እንዴት ያለህ ደፋር

ሰው ነህሳ!?» አሉት።

ዘይድ ለተወሰኑ ቀናት መዲና የነቢን ሰዐወ ኮቴ እየተከታተለ

ካሳለፈ በኋላ የቀዬውን ሰው ከዲኑ ሊያቀላቅል መዲናን ትቶ

ወጣ።

እሱን ሊሸኙ የወጡት ነብይም የአሸዋው አዋራ ከአይናቸው

እስኪሰውረው ድረስ እየተመለከቱት፦«ወይ ዘይድ! የመዲናን

ወረርሽኝ ባልፈራለት ኖሮ እዚህ ተቀምጦ ስንት እና ስንት ጀብድ

ይፈፅምልኝ ነበር» አሉ።

ዘይድ ከጓደኞቹ ጋር ሁኖ የመዲናን ግዛት ትቶ ወጣ። መዲና ላይ

በተከሰተው ወረርሽኝ ዘይድ መለከፉን ሳያውቅ ከአሸዋማው ሜዳ

ላይ ህመሙ ያጥወለውለው ጀመር።

ሞትን ተሽቀዳድሞ የዲኑን ብርሀን ለቀዬተኛው ሊያደርስ ከሞት

ጋር ቢፎካከርም ከተወሰነለት ሰአት ቅፅበትን የማይዛነፈው ሞት

ዘይድን የመጨረሻዋን ትንፋሽ አስተነፈሰው።

በኢስላም ጥላ ስር ከመግባቱ በፊት የፈፀማቸውን አያሌ

መልካም ስራዎች አላህ ሊመነዳው መዲና አምጥቶ ከነቢ

ካገናኘው በኋላ ምንዳውን ሊያስረክበው ከራሱ አገናኘው።

____

ምንጭ፦

ﺍﻹﺻﺎﺑﺔ

ﺍﻻﺳﺘﻌﻴﺎﺏ

ﺗﻬﺬﻳﺐ ﺍﺑﻦ ﻋﺴﺎﻛﺮ

ﺛﻤﺎﺭ ﺍﻟﻘﻠﻮﺏ

ﺣﻠﻴﺔ ﺍﻷﻭﻟﻴﺎﺀ

image
Send as a message
Share on my page
Share in the group