Translation is not possible.

የባህሪ ለውጥ ምክንያቶች

~

አንዳንዴ ለዘመናት በመልካምነት የምናውቃቸው ሰዎች የማናውቃቸው እስከሚመስለን ድረስ ባህሪያቸው ተቀይሮ ለመሸከም የሚከብዱ ይሆናሉ። ምክንያቱ ምን ይሆን? የችግሮቹን መንስኤዎች ማወቅ ለማስታመም፣ ለማለፍ፣ ለመረዳት፣ ... ያግዘናል። የሰዎችን ባህሪ ከሚቀይሩ ነገሮች ውስጥ የሚከተሉት ተጠቃሽ ናቸው።

1- ስልጣን፦

ስልጣንና ኃላፊነት ሲያገኙ የሚቀየሩ ብዙ ሰዎች አሉ። የሚያውቁትን እንደማያውቁት ይሆናሉ። ንቀትን ንቃት ያደርጋሉ። ውለታ ይረሳሉ።

2- ስልጣን ማጣት፦

ከስልጣንና ኃላፊነት ሲነሱ በብስጭት፣ በቁጭት እየተብከነከኑ ለሩቁ ቀርቶ ለቅርብ ሰዋቸው ጭምር ባህሪያቸው የሚፈትኑ ይኖራሉ።

3- ሃብት፦

ትሁትና ደግ የነበሩ ሰዎች ሃብት ካገኙ በኋላ ትእቢት፣ ንቀትና ኩራት የሚባሉ ነውሮችን ጌጥ የሚያደረጉ የዋሆች አሉ።

4- ድህነት፦

አግኝቶ ማጣት ትልቅ ህመም አለው። ድህነት ሲዳብሳቸው መልካም ባህሪያቸው ከገንዘባቸው ጋር ጥሏቸው የሚጠፋ ሰዎች አሉ። መቼም አመላችን እንደ መልካችን ብዙ አይነት ነው።

5- ሱስ፦

በሱስ በመጎዳታቸው የተነሳ ከጊዜ ጊዜ ትእግስት እንደ ቁምጣ እያጠራቸው የሚሄድ፣ ይሉኝታ የማያውቁ፣ "ሰው ምን ይለኛል?" የማይገዳቸው ሰዎች ቁጥራቸው ከብዙም የበዛ ነው።

6- ሃሳብ፦

የሰው ልጅ በህይወቱ ለተለያዩ ሃሳቦች መጋለጡ የሚጠበቅ ነው። የሃሳብ መደራረብ፣ የአእምሮ መወጠር ደግሞ የሰው ባህሪ ላይ ግልፅ ተፅእኖ ያሳድርበታል።

7- ህመም፦

ህመም ባህሪን ይቀይራል። ያነጫንጫል። ከሰው ቀርቶ ከእንስሳ፣ ከግድግዳ ጋር ሁሉ ያጋጫል።

8- እርጅና፦

እርጅና እንደ ልጅ ያደርጋል። እንዲያውም ሊብስ ይችላል። ልጅን ተቆጥተህ ታስደነግጠዋለህ። ከእርጅና ጋር የሚመጣ ክፉ ባህሪ ግን ለገላጋይ አይመችም። እርጅና ላይ ሌሎች ገፊ ችግሮች ሲደረቡበት ደግሞ በቡሃ ላይ ቆረቆር ይሆናል።

ምንጭ፦ አብዛኛው ሃሳብ ከሸይኽ ዐብደላህ አልፈውዛን (ሚንሐቱል ዐላም፡ 10/295 - 296) የተወሰደ ነው።

Ibnu Munewor

Send as a message
Share on my page
Share in the group