Translation is not possible.

የመኳረፍ አደጋዎች

~

መኳረፍ የሚያስከትላቸው ብዙ አደጋዎች አሉት። በዚህም የተነሳ ነብዩ ﷺ ሙስሊሞች እርስበርሳቸው ከሶስት ቀን በላይ እንዳይኳረፉ አሳስበዋል። በተጨባጭ ዲናዊ ጉዳይ መነሻ የሚኖርን ማኩረፍ በተመለከተ በተገቢነቱም ላይ ሆነ በቆይታው ላይ ለመወሰን የራስን ስሜት ወደ ጎን በማድረግ ጥቅምና ጉዳቱን ማስላት ያስፈልጋል። በዱንያዊ ጉዳይ ላይ የሚገጥምን መቀያየም በተመለከተ ግን ከሶስት ቀን ያለፈ መኮራረፍ ጥብቅ ክልከላ የመጣበት ጉዳይ ነው። ብዙ የሚከተሉት መዘዞችም ይኖራሉ። የተወሰኑትን ልንቀስ፦

1. የተኳረፉ ሰዎች የሚሰሩት መልካም ስራ ወደ አላህ አይወጣም። ይሄ እጅግ ከባድ የሆነ የኩርፊያ ውጤት ነው። ነብያችን ﷺ እንዲህ ይላሉ፦

تُفْتَحُ أَبْوَابُ الْجَنَّةِ يَوْمَ الِاثْنَيْنِ وَيَوْمَ الْخَمِيسِ، فَيُغْفَرُ لِكُلِّ عَبْدٍ لَا يُشْرِكُ بِاللَّهِ شَيْئًا، إِلَّا رَجُلًا كَانَتْ بَيْنَهُ وَبَيْنَ أَخِيهِ شَحْنَاءُ، فَيُقَالُ : أَنْظِرُوا هَذَيْنِ حَتَّى يَصْطَلِحَا، أَنْظِرُوا هَذَيْنِ حَتَّى يَصْطَلِحَا، أَنْظِرُوا هَذَيْنِ حَتَّى يَصْطَلِحَا ".

“የጀነት በሮች ሰኞ ቀንና ሐሙስ ቀን ይከፈታሉ። ከዚያም ለያንዳንዱ በአላህ ላይ ምንም የማያጋራ ሙስሊም ምህረት ይደረግለታል። በእሱና በወንድሙ መካከል ጥላቻ (ቂም) ያለበት ሰው ሲቀር። ‘እነዚህን እስከሚታረቁ ድረስ አቆዩ’ ‘እነዚህን እስከሚታረቁ ድረስ አቆዩ’ ይባላል።” [ሙስሊም፡ 2565]

2. መኳረፍ ከዲን ይዘጋል። መመካከር (ነሲሐ) በሐዲሥ ዲን (ኢስላም) ተብሎ እንደተገለፀ አስታውሱ። የተኳረፈ ሰው ይህንን ዲን ሊተገብር አይችልም።

3. መኳረፍ አንድ ሙስሊም በሌላው ላይ ያለውን ሐቅ እንዳይውወጣ በር ይዘጋል። ሲገናኙ ሰላምታ ማቅረብ፣ ቢታመሙ መጠያየቅ፣ ሀዘን ቢደርስ ማፅናናት (ተዕዚያ መድረስ)፣ በድግስ ላይ መጠራራትና መገኘት፣ ቢሞቱ ጀናዛ ላይ መስገድ፣ መሸኘትና መቅበር ይቀራል መኮራረፍ ሲኖር። ይሄ በጣም ከባድ ነገር ነው።

4. መኳረፍ ሌላም ፀያፍ ነገር አለው። ያኮረፉት ሰው በሚገጥመው ችግር መደሰት፣ በሚያገኘው መልካም ነገር ደግሞ ማዘንና መከፋትን ያስከትላል። ይሄ ከኢስላማዊ አደብ በእጅጉ የራቀ ዘግናኝ ጥፋት ነው።

5. መኳረፍ ያኮረፉት አካል በሚቸገር ጊዜ ከጎኑ እንዳይቆሙ ያግዳል። የተኮረፈው አካል ወላጅ፣ እህት፣ ወንድም፣ ቅርብ ቤተሰብ ሲሆን የሚኖረውን መቆራረጥ ደግሞ አስቡት። “ዝምድናን ቆራጭ ጀነት አይገባም” የሚለውን አስታውሱ።

6. መኮራረፍ አንዱ ሌላውን መስደብ፣ ማማት፣ ሚስጥር ማውጣት፣ በውሸትም በእውነትም ማነወርና ስም ማጥፋት ይከተለዋል። ይሄ ደግሞ ከከባባድ ወንጀሎች ውስጥ የሚቆጠር ሌላ ተደራቢ ጥፋት ነው።

(የቡሉጉል መራም ሸርሕ ከሆነው ሚንሓቱል ዐላም ኪታብ፡ 10/114 የተወሰደ)

ኢብኑ ሙነወር

=

የቴሌግራም ቻናል፡-

https://t.me/IbnuMunewor

Telegram: Contact @IbnuMunewor

Telegram: Contact @IbnuMunewor

كناشة ابن منور
Send as a message
Share on my page
Share in the group