Translation is not possible.

የፍልስጤም ታሪክ

ምዕራፍ -2

እስራኤል ክፉ ፅንስ

ክፍል-6

[ተፃፈ-በአብዱልከሪም ሙሐመድ]

የመጀመሪያው ፍልስጤምን ለሁለት የመክፈል እቅድ የተዘጋጀው ብዙ ደም ያፋሰሰውን የ1936ቱን ታላቅ አመፅ ተከትሎ ነበር፡፡ በጁን 7/1937 የአረቦችንና የአይሁዳዊያን ፍላጎት ለማመላከት በሎርድ ቢል በቀረበው ሪፖርት መሠረት ያደረገ ነበር፡፡

እንግሊዝ ለአይሁዳዊያን ቃል የገባችላቸውን በሙሉ የፍልስጤም ምድር (እንደውም አንዳንድ ፅዮናውያን ዮርዳኖስን ጭምር ታሰቦላቸው እንደነበር ይናገራሉ) ሀገር የመመስረት ህልም ከንቱ ምኞት ሆኖባታል፤ አረቦች ሚያልሙትን አረባዊ ህብረት ተመስርቶ ከባድ ተቀናቃኝ ከሚፈጠር ደግሞ እንግሊዝ ሞቷን ትመርጣለች፡፡

በዚህም ደህና ሲታጣ ይመለመላል ጎባጣ እንዲሉ አስታራቂ ሃሳብ የሚመስል ሌላ ህልም በ ‹ግጭት ፈቺ› ኮሚቴው ታቀደ፤ የሁለቱ ጉዳይ ፍልስጤምን በመከፋፈል ካልሆነ በቀር ለመፍታት ማይቻል መሆኑን አመላከተ፡፡

የእቅዱ ዝርዝር ሀተታ እንደሚከተለው ነው ፡

1ኛ አይሁዳዊት ሀገርን በፍልስጤም መመስረት ሲሆን ግዛቷም ከሰሜንና ምዕራብ ክፍል ከሊባኖስ ድንበር እስከ ደቡብ ጃፍፋ (እነ ኤከር፣ሀያፋ፣ሳፋድ፣ጠበርሪያህ፣ናዛሬትና ቴል-አቪቭን) ያጠቃልላል፡፡

2ኛ ቅዱስ ስፍራዎችን (ቤተልሔም እና አል-ቁድስ (እየሩሳሌም)) በሞግዚቷ አንግሊዝ ቁጥጥር ስር እንዲሆኑና ከ ጃፍፋ፣አሉድ፣አል-ራምላ፣ናዝሬት የመሳሰሉ ከተሞች ጋር የሚያገናኝ መንገድ መስራት፡፡

3ኛ አረባዊት ሀገርን ደግሞ በደቡብና ምስራቅ ቦታዎች ላይ (ጃፍፋ ከተማን ጨምሮ እስከ ምስራቅ ዮርዳኖስ ድረስ) መመስረት፡፡

4ኛ አይሁዳዊቷ ሀገር ለአረባዊቷ የገንዘብ ድጋፍ እንድታደርግ እንዲሁም እንግሊዝ አንድ ሚሊዮን ስተርሊንግ ለዚች መሬት ለተወሰደባት መስጠት፡፡

5ኛ የሰዎች ልውውጥ ማለትም በአዲሲቷ ሀገር የሚገኙትን ወደ 325 ሺህ የሚሆኑ አረቦችን ወደ አረባዊቷ ሀገር ማዘዋወር እና እዛም ቦታዎችን ለነሱ ማመቻቸት፡፡

6ኛ ወደ ሁለቱ ሀገራት በሚገቡ እቃዎች ላይ ቀረጥን በጋራ ለመሰብሰብ ስምምነት ላይ እንዲደረሱ ማድረግ የሚሉት ናቸው፡፡

ሆኖም ይህ በፍልስጤዊያን ዘንድ ሌላ ቀልድ እየተቀለደባቸው እንደሆነ በማወቃቸው ሊስማሙ አልቻሉም፡፡ መቼም አንድ የሰፈር ጉልቤ አንድን ሰው በቤቱ መጥቶ የሚጋፋው ባዳ (ለዛውም በሀይማኖትም ይሁን በምንም የማይገናኝ) ጋር ውርስ ተካፈል ቢለው እምቢታው የሚያስገርም አይደለም፡፡ ይህ አለመስማማት ምክንያት ሀሳቡን እንዳይተገበር እንቅፋት ሆኖ ቆየ፡፡

በኖቬምበር 23 1938 የእንግሊዝ ቀኝ-ግዛቶች ሚኒስትር በዚህ ጉዳይ ላይ ወሳኝ የሆነን ንግግር ሲያስቀምጥ ማኅበረሰቡ ከአረቦች እይታ አንፃርም ሆኖ ነገሮችንም እንዲያይ አድርጎት ነበር፡፡

በመካከለኛው ዘመን አይሁዳዊያን በአውሮፓ ውስጥ ይደርስባቸው የነበረውን ግፍና ጭቆና እንዲሁም ጥገኝነትን የፍልስጤምን ዋጋ በመክፈል ማካካስ ትክክል እንዳልሆነ እና ከብዙ ዘመናት በፊት የሰፈሩት አረቦች አስተያየት ሳይጠየቅ የባልፎር ቃልኪዳን መግባት ትልቁ ስህተት እንደሆነ በግልፅ አስቀምጧል፡፡

በተጨማሪም የ20 ዓመት የጦርነት ገፈት ቀማሽ የሆነው፣ የመሬት ወረራን በባዕድ ህዝቦች የሚካሄድበት አረብ ተቃውሞውን በደማቅ እሳት ማሳየቱ እጣውም በራሳቸው መሬት ላይ ለሌላ አዲስ ማህበረሰብ ተገዢ ሆኖ እንዳይኖሩ መስጋታቸው ጥፋት አለመሆኑን አፅንኦት ሰጥቷል፡፡

ከዚህ ንግግሩ በኋላ ለንደን ኮንፈረንስ ላይ ላይ የግብፅ፣ ኢራቅ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የመን፣ ምስራቅ ዮርዳኖስ ሰዎች ከፍልስጤማዊያንና አይሁዳዊያን በተጨማሪ ተገኝተው ነበር፡፡

ሆኖም በፌብሯሪ 7 1939 የክቡ ጠረጴዛ ኮንፈረንስ በጭቅጭቅ ያለ ስምምነት አለፈ፡፡ ከጊዜያት በኋላ የእንግሊዝ መንግስት ‹ነጩ መፅሀፍ› በሚል የሰየመውን ረቂቅ ሀሳብ ለተሳታፊዎቹ አስተዋወቀ፡፡ በዚህ ሀሳብ ላይ ለመወያየትና ተግባራዊ ለማድረግ እየታቀደ እያለ ነበር ሁለተኛው የአለም ጦርነት የተቀሰቀሰው፡፡

ምዕራፍ 2 በዚሁ ተጠናቀቀ፡፡

Send as a message
Share on my page
Share in the group