Translation is not possible.

ትንሹ ዒድ ባህላዊ በዓል ወይስ እንደ አምልኮ ዘርፍ የተያዘ ቢድዐ?!

—————

ከዒደል ፊጥር ማግስት ጀምሮ የሚፆመውን 6ቀን የሸዋል ፆምን ተከትሎ ዒደል ፊጥር በወጣ በሳምንቱ የተወሰኑ ሙስሊሞች ዘንድ የሚከበር የሸዋል ፍቺ ወይም ትንሹ ዒድ በመባል የሚታወቅ በዓል አለ። ይህ በዓል እንደ ሸሪዓ ምንም አይነት ማስረጃ የሌለው በዋናነት ወደ ደቡብ ያሉ የተወሰኑ ብሔረሰቦች ዘንድ የሚከበር መሰረተ ቢስ የሆነ በዓል ነው። በተለይ አላህ ምንም አይነት ማስረጃን ያላወረደበት ይህ በዓል ስልጤ፣ ጉራጌና ሀረሪ ብሔረሰብ ዘንድ በልዩ ሁኔታ የሚከበር በዓል ነው። ዲናችን ሙሉ ነው። ከሁለቱ ዒድና ከሳምንታዊ ጁምዓ ውጪ ምንም ይሁን ምን አዲስ ፈጠራ (ቢድዐ) ነው። በዲናችን ላይ አዲስ ፈጠራ ሁሉ ደግሞ ጥመት ነው። የአላህ መልእክተኛ (ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) በየ ሳምንት ጁምዓ ኹጥባቸው ላይ እንዲህ ይሉ ነበር:-

«…የነገሮች ሁሉ ሸር ማለት (በዲን ላይ) አዲስ ፈጠራ ነው፣ አዲስ ፈጠራ (ቢድዐ) ሁሉ ጥመት ነው» ሙስሊምና ነሳኢይ የዘገቡት ሲሆን፣ ነሳኢይ «ጥመት ሁሉ የእሳት ነው» የሚል ዘገባ ጨምሯል፣ ሰነዱም ሶሂህ ነው።

ይህ በዓል ከላይ የጠቀስኩላችሁ ብሔረሰቦች ዘንድ የሚከበር መሰረቱ ገጠር የነበረ ቢሆንም ከጊዜ ወዲህ ግን በየ ከተማውም በተለየ መልኩ ሌሎች ብሔረሰቦችም ተሳትፈውበት መከበር ጀምሯል። ለበዓሉም ልክ እንደሌሎች በሸሪዓ እንደተጠቀሱ በዓሎች (እንዲያውም በበለጠ መልኩ) የተለያዩ ዝግጅቶች ሲደረጉ ይስተዋላል። ታዲያ ማስረጃ የሌለው በዓል እስከሆነ ድረስ ምንም ይሁን ምን፣ መውሊድን ጨምሮ መላው የአለማችን ህዝብ ቢያከብረው እንኳን ቢድዐ ከመሆን አይወገድም!!። ቢድዐ ደግሞ ጥመት ነው፣ ጥመት ሁሉ የእሳት ነው።

በትንሹ ዒድ ላይ አንዳንድ ስለ ዲናቸው ግንዛቤ አላቸው የሚባሉ፣ ሸሪዓው ከሚያግራራው ውጭ እያግራሩ ህዝብ ዘንድ ተደማጭነት ለማግኘት የሚዳክሩ ሰዎች የሚያነሱት ብዥታ አለ። እሱም "ምን ችግር አለው? ቢከበር ባህል ነው እንጂ ሃይማኖታዊ ይዘት የለውም" ይላሉ።

መልስ:-

1ኛ, ባህላዊ በዓል ቢሆንስ በዚህ መልኩ በየ አመቱ እየጠበቁ በድምቀጥ ማክበሩን ማን ፈቀደው?

የሙስሊሞች ሸይኽ በመባል የሚታወቁት ታላቁ ሊቅ ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚየህ (ረሂመሁላህ) የሸዋልን ስምንተኛውን ቀን እንደ በዓል አድርገው የሚይዙና (የደጋጎች ዒድ) ብለው የሰየሙ ሰዎችን አስመልክተው እንዲህ ይላሉ:-

(وأما ثامن شوال : فليس عيداً لا للأبرار ولا للفجار , ولا يجوز لأحد أن يعتقده عيداً, ولا يحدث فيه شيئاً من شعائر الأعياد ) ا. هـ. الاختيارات الفقهية ص/199

“የሸዋል ስምንተኛው ቀንማ ለደጋጎችም ሆነ ለጠማሞች ዒድ አይደለም!። ለአንድም ሰው እለቱን ልዩ የመደሰቻ ዒድ ቀን አድርጎና አምኖ መያዝ አይፈቀድለትም!። በእለቱም ምንም አይነት ለዒድ ከሚንፀባረቁ ነገሮች ማንፀባረቅ አይፈቀድለትም!።” [አል-ኢኽትያራት አል-ፊቅሂየህ 199]

ታላቁ የኢስላም ሊቅ ኢምሙ ዐብዲልዐዚዝ ቢን ባዝ (ረሂመሁላህ) በውስጣቸው ሸሪዓን የሚፃረር ነገር ባይኖርባቸው እንኳን እንደ ባህል (ልማድ) ተደርገው የሚከበሩ በዓላትን በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱ እንዲህ ይላሉ:- “ከሁለቱ ዒዶች ውጪ ማንኛውንም ዒድ አድርጎ መያዝ አይፈቀድም!። የእርዱ ቀን ዒድ (ዒደል አድሃ) እና ዒደል ፊጥር፣ እነዚህ ናቸው የሙስሊሞች ዒድ ማለት። እንዲሁም በየ ሳምንቱ የሚመጣው የሚሰገድበት እለተ ጁም ነው። በተረፈ በየ አመቱ የሚሽከረከር የሚሰባሰቡበት የሆነን ዒድ መያዝ መሰረት የሌለው ተግባር ነው። ከነቢዩ  (ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) በኋላ ሶሃቦችም ይሁኑ ታቢዒዮች 3ቱ ክፍለ ዘመናት ውስጥ የነበሩ ትውልዶችም እንዲህ ያሉ በዓላትን አላከበሩም!። በኛ ላይ ግዴታው እነሱ የተጓዙበትን መከተልና በመንገዳቸው መጓዝ ብቻ ነው… ሰዎች መልካም ነው ብለው የሚያስቡት የሚደጋገም ባህል ካላቸው ሀቁን ካወቁና ከተረዱ በኋላ ያንን ባህል መተው ግዴታ ይሆንባቸዋል…” [የሸይኹ ዌብሳይት ላይ በድምፅም በፅሁፍም አለ።]

2ኛ, እንደ አምልኮ ዘርፍ ነው የሚይዙት።

2.1, ለዒደል ፊጥ ከሚያደርጉት ዝግጅት የበለጥ ለዚህ ቀን ነው  የሚዘጋጁት።

2.2, በዋናናት አባቶችና እናቶች የሸዋልን 6ቀን አከታትለው የሚፆሙት የዚህን ቀን ፍቺ ለማክበር ነው።

2.3, በተጋነነ መልኩ ለዒደል ፊጥር ሀይላቸውን ቆጠብ አድርገው ለዚህ ቀን ግን ሀይላቸውን አሟጠው ይጨርሱና ከፊታችን ለሚመጣው ዒደል አድሃ እንኳን በቂ ዝግጅት አያደርጉም። ለዚህም ነው ታላላቅ የኢስላም ሊቃውንቶች "አንድ ቢድዐ በተተካ ቁጥር ሌላ አንድ ሱንና ይሰርዛል" የሚሉት።

2.4, ዝግጅቱን በዋናነት የሚያከብሩ ሰዎች ሲጠየቁ የሸዋል 6ቀን ፆም ፍቺ (ዒድ) ነው ብለው ነው የሚናገሩት እንጂ ባህል ነው የሚል አመለካከት የላቸውም። ይህ (ባህል ነው) የሚለው አመለካከት ጠንካራ አቋም ያላቸው የሱና ሰዎች "ትንሹ ዒድ ቢድዐ ነው" ብለው ሲያስጠነቅቁ እነ ሸህ ገራገር ህዝቡ ዘንድ ተወዳጅነት ለማግኘት ሲጠየቁ የፈበረኩት አመለካከት ነው። ይህን አመለካከት ሲፈበርኩ ግን ይህን ሁሉ እውነታ ያውቁታል። እያወቁ ሀቁን ይደብቁታል፣ ያምታቱታል። ይህ ደግሞ አላህ እንዲህ በማለት አይሁዶችን የወቀሰበት አደገኛ ተግባር ነው:-

وَلَا تَلْبِسُوا الْحَقَّ بِالْبَاطِلِ وَتَكْتُمُوا الْحَقَّ وَأَنتُمْ تَعْلَمُونَ

«እውነቱንም በውሸት አትቀላቅሉ፡፡ እናንተም የምታውቁ ስትሆኑ እውነትን አትደብቁ፡፡» አል-በቀረህ 42

3ኛ, እንዲህ ያሉ በዓላት ላይ ሌላው ከባድ አደጋ!! የተለያዩ የኢስላምና የሙስሊሙ ጠላቶች እንዲህ ያሉ አዳዲስ በዓላትን ቀንና መስለው በተለየ መልኩ በየ ሚዲያዎቻቸው እያስተዋወቁ ሙስሊሙ በሀይማኖቱ ከተደነገጉ ብርቅዬ በዓላት እንዲዘናጋና ከሀይማኖቱ ተቃራኒ መንገድ እንዲጓዝ ይሰራሉ።

ወላሁ አዕለም!!

Send as a message
Share on my page
Share in the group