Табасаранан алхьа кха дац.

አንድ ሬስቶራንት አስቸኳይ የሽያጭ ማስታወቂያ ግርግዳው ላይ ለጠፈ

"ከነሙሉ ዕቃው የሚሸጥ ምግብ ቤት" ይላል ባነሩ ላይ በትልቁ የተፃፈው።

"ከሬስቶራንቱ ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ጋዛ ላሉ ወገኖቻችን መድኃኒት መግዣ ይውል ዘንድ ሙሉ በሙሉ ለፍልስጤም ቀይ ጨረቃ ይለገሳል"

ረቢሐል በይዕ! ያማረ ሽያጭ! ትርፋማ ንግድ!

ክስተቱ ታሪክን የኋሊት አስታወሰኝ።

ረሱሉል አሚን ከባልደረቦቻቸው ጋር በተቀመጡበት አንድ ወጣት እየተንደረደረ ስሞታውን ሊያሰማ ወደ ውስጥ ዘለቀ

"የአላህ መልእክተኛ ሆይ" በማለት ንግግሩን ጀመረ "የአትክልት ስፍራዬን እያጠርኩ ነበር። የጎረቤቴ አንዲት የዘንባባ ዛፍ መሐል ላይ ተጥዳ አገደችኝ። አጥሩ ይስተካከልልኝ ዘንድ በነፃ እንዲተውልኝ ወይም እንዲሸጥልኝ ጠየቅኩት እሱ ግን ፈቃደኛ አልሆነም" በማለት የአላህ መልዕክተኛ ጎረቤቱን አስጠርተው እንዲጠይቁለት ስሞታውን አቀረበ።

የአላህ መልዕክተኛ ፊት ቀርቦ ዘንባባውን እንዲተውለት ወይም እንዲሸጥለት ውዱ ነቢ ቢጠይቁት አልሸጥም አልሰጥም በሚለው እንቢታው ፀና

"የዘንባባውን ዛፍ ሽጥለት። ለአንተ በምትኩ ጀነት ውስጥ ፈረሰኛ በጥላዋ መቶ አመት የሚጋልባት ዛፍ ይኖርሀል" አሉት። አሁንም ሰውየው በአቋሙ ላይ መሆኑን የአላህ መልእክተኛ ባልደረቦች አይተው ተገረሙ። አንድ ሰሐባ ከመሐላቸው ተነሳ። አቡ ደህዳህ ይሰኛል። "ያን የዘንባባ ዛፍ ገዝቼ ለወጣቱ ብሰጠው በጀነት ውስጥ የዘንባባ ዛፍ ይኖረኛልን" ሲል የአላህ መልዕክተኛን ጠየቀ በአግራሞት ሰውየውን እየተመለከተ። መልእክተኛውም "አዎ" ብለው መለሱለት ወደ ሰውየው ዞረና "የእኔን የአትክልት ስፍራ ታውቀዋለህን?" አለው።

ሰውየውም "አዎ በከተማው ውስጥ ስድስት መቶ የዘንባባ ዛፍ ያለበት፣ ውቡና ረጅሙ ቤት ያረፈበት፣ በጣፋጭ የውሀ ምንጭ ጉድጓድ የተሞላ፣ ዙሪያው በተስተካከለ ግንብ የታጠረን የአቡ ደህዳህን የአትክልት ስፍራ የማያውቅ ማን አለ? ቴምሩ ከፍተኛ ጥራት ያለው በመሆኑ የከተማይቱ ነጋዴዎች ሁሉ ፍሬዋን ይናፍቃሉ" አለ።

አቡ ደህዳህ "አንዲት የዘንባባ ዛፍህን በአትክልት ቦታዬ፣ በቤተ መንግስቴ፣ በጉድጓዴና በተስተካከለው አጥሬ ሽጥልኝ" ሲል ጠየቀው። ሰውየው ወደረሱል ተመለከተ ግራ ገብቶት አይኖቹን አንከራተተ። ስድስት መቶ የዘንባባ ዛፎችን ያውም የከተማው ምርጥ የቴምር ፍሬ የሚበቅልበትን የአትክልት ስፍራ በአንዲት ዛፍ የመቀየር ጥያቄው አልዋጥለት ብሎ ፈዘዘ። አቡ ደህዳህ በደስታ እየተፍለቀለቀ ረሱልና ሰሐቦች የተጣዱበት አስገራሚው ሽያጭ ተጠናቀቀ።

አቡ ደህዳህ ወደ አላህ መልእክተኛ በትኩረት እየተመለከተ "የአላህ መልእክተኛ ሆይ በጀነት ውስጥ የዘንባባ ዛፍ አለኝ አይደል?" አለ የአላህ መልእክተኛ "ላ በፍፁም" አሉ። የአቡ ደህዳህ አይኖች በትካዜ ፈጠጡ ረሱል ንግግራቸውን ቀጠሉ "አላህ ቸርነትህን አይቶ በጀነት ውስጥ ከብዛታቸው የተነሳ ልቆጥራቸው በማትችላቸው የዘንባባ ዛፎች ተክቶልሀል እሱ ልግስናው የሰፋ የቸሮች ሁሉ ቸር የሆነ ጌታ ነውና

መልእክተኛው ንግግራቸውን እየደጋገሙ ለአቡ ደህደህ አላህ የተካውን የዘንባባ ዛፍ ብዛት ሲያወሩ ሰሐቦች ተደንቀው የአቡ ደህዳህን ደረጃ ተመኙ። በደስታ ተውጦ ቃሉን ተግባራዊ ለማድረግ እየተጣደፈ ወደ ቤት አቀና። ግቢው በር ላይ እንደደረሰ ሚስቱን ተጣራ። ከበሩ ብቅ አለች።

"የአትክልት ቦታውን፣ መኖርያ ቤቱንና፣ የውሀ ጉድጓዱን ከነ አጥሩ ሸጥኩት" አላት። ሚስት የባሏን የአነጋገድ ስልት ልምዱንና ብልህነቱን ታውቅ ነበርና ተደሰተች። በስንት ዋጋ እንደሸጠውም ጠየቀች። እርሱም "ዕቃችንን ሸክፈን ዛሬውኑ ይህንን ቤት ለቀን እንወጣለን። ፈረሰኛ በጥላዋ መቶ አመት በሚጋልባት የጀነት ዛፍ ሽጬዋለሁ" ሲላት በእልልታ ቤቱን እያቀለጠች "አቡ ደህዳህ በግብይይቱ አተረፈ" እያለች ደጋገመች።

image
Send as a message
Share on my page
Share in the group