Translation is not possible.

አንዳንድ ንግግሮች አሉ ከአላህ ዘንድ አጅር የማናገኝባቸው፤ ለስኬትም የማንበቃባቸው፡፡ ለዱንያችን የማይጠቅሙን ፣ ለአኺራችንም የማይፈይዱን ፣ ወደ ጀነት የማይመሩን ከእሣትም የማያድኑን፡፡ ወይ ዚክር ሆነው አላህን አላወሳንባቸው ወይ ደግሞ ሹክር አይደሉ አምላካችንን አላመሰገንባቸው፡፡

የዚህ ዓይነቶቹ ወሬዎችና ንግግሮች ‹ማላ የዕኒ› ይላቸዋል እስልምና፡፡ የማይመለከቱን ጉዳዮች፣ ዝባዝንኬዎች፣ አሉባልታዎች፣ እንቶፈንቶዎች፣ እርባና ቢስ ጉዳዮች ልትሏቸው ትችላላችሁ፡፡ ወዳጆቼ … በዚህ ዓይነቱ ማዕድ ላይ ድንገት ከገባችሁ እንኳን ብዙ አትቆዩ፤ ቁምነገር ካጣችሁና ጥቅሙ ካልታያችሁ ቶሎ ዉጡ፡፡ ጊዜያችሁ ይቃጠላልና፡፡ ትልቁን ሀብታችንን ጊዜን አቃጠልን ማለት ትልቅ ኪሣራ ላይ ወደቅን ማለት ነው፡፡ መውደቅ በኃጢአት ብቻ አይደለም፤ በተጨመረ ዕድሜ ላይ ምንም መልካም ነገር ሳይጨምሩ መዋልም መዉደቅ ነው፡፡

ሳያጣሩ መረጃን ማሠራጨት፣ የሰሙትን ነገር ሁሉ ለማውራት መቸኮል፣ በማያገባ ነገር ገብቶ መፈትፈት፣ እዚህም እዚያም ሄዶ መከራከር … ሌላው የጊዜው ማላ የዕኒ ነው፡፡ ዛሬ ላይ ማንን መስማት እስኪያቅተን ድረስ ሁሉም ተንታኝ ሆኗል፡፡ የሚችለውም የማይችለውም፣ የሚያገባውም፣ የማያገባውም ይናገራል፡፡ የዚህ ዓይነቱ ባህሪ የጥሩ ሙስሊም መገለጫ አይደለም፡፡

እናም ወዳጆቼ … ለጊዜያችን በትልቁ እንጨነቅ፡፡ እያንዳንዷን ሰከንድ በምን ላይ እንዳዋልናት መለስ ብለን እንቃኝ፡፡ መዝናናት መቀለዳችንም በልክ ይሁን፡፡ መልካም ሥራችን ይብዛ ይክበድም፡፡ የነገ ሥራችን ይመዘናል እንጂ አይቆጠርም፡፡ ከመልካም ሥራ በላይም ምንም ዋስትና የለንም፡፡

አምላካችን ሆይ!አንተን በማውሳት፣ በማመስገንና አምልኮህን በማሳመሩ ላይ እርዳን 🤲

image
Send as a message
Share on my page
Share in the group